የክርስቶስ ተከታዮች በግልም ሆነ በማኅበር በዓለም ውስጥ ናቸው፤ ከዓለም ግን አይደሉም። ዓለምን በወንጌል ስብከት ሊለውጡ እንጂ በዓለም ሊለወጡ አይጠበቅባቸውም [ዮሐንስ 17፡14-19። ሮሜ 12፡1-2]። ቤተክርስቲያን አንዴ በምድራዊ ሥልጣን ዙሪያ ስትወዛገብና ከሥልጣናት ጋር ስትወሳሰብ፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ ምድራዊውን ጨርሶ ስትዘነጋ ታይታለች። እንደ መሪዎቿ አስተዋይነትና ለዘብተኛነት ጠቃሚና ጎጂ የሆኑ መንፈሳዊና ማኅበራዊ ውጤቶችንም አስመዝግባለች። ለምሳሌ፣ በ1980ዎቹ አጋማሽ ጨቋኝ አገዛዞችን ለመገርሰስ በፖላንድና በሃንጋሪ የተቀጣጠለው የነጻነት ችቦ የተለኮሰው በ[ካቶሊካዊት] ቤተክርስቲያን ነበር። ቤተክርስቲያን ማኅበረሰባዊ ድርሻዋ እስከምን ድረስ ነው? ፖለቲካ ምንድነው? መንፈሳዊነትስ? ሃይማኖትና መንግሥት የተለያዩ ናቸው፤ አንዱ በሌላው ጉዳይ ጣልቃ አይገባም ሲል ምን ማለቱ ነው? ከዓለማዊ አኗኗርና አሠራር የተለዩ ሆኖ የክርስቶስን ማኅበር ዓይነተኛነት በዓለም ላሉት እንደ ዘላቂ አማራጭ ለማቅረብ እንዴት ይቻላል? የቤተክርስቲያን ተቀዳሚ ተልእኮ ምንድነው? አማንያን በግልና በማኅበር ምስክርነታቸው እንዳይጎድፍ ምን ጥንቃቄ ይውሰዱ? ቤተክርስቲያንስ እንደ አንድ ድርጅት በወቅቱ ፖለቲካ ውስጥ መሳተፏና ማኅበረ ምእመኗን ማሳተፏ ተገቢ ነው? በፖለቲካ ቀጥተኛ ተሳትፎ ማድረግ ለሁሉም ይሆናል ወይ? ከወንጌል እውነትና ከፍትኅ ጋር መቆምና መራመድ ማለት ምን ማለት ነው? እነዚህ ዋነኛና አነጋጋሪ ጥያቄዎች ናቸው። ወንድም ተስፋዬ ሮበሌ አንዱን አመለካከት ይዞልን ቀርቧል። በቀረበው ጽሑፍ ላይ ተጨማሪ ወይም የተለየ አሳብ ካላችሁ በ”ወርድ” ፋይል በ This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. ላኩልን። ከአዘጋጁ።
ክርስቲያን በፖለቲካ ውስጥ በንቃት መሳተፍ ይኖርበታልን?
በተስፋዬ ሮበሌ
በአንድ መስቀለኛ መንገድ ላይ በየቀኑ አሠቃቂ አደጋ ይከሠታል፤ ከአደጋው የተነሣም በርካታ ሰዎች ይሞታሉ፤ ከፍተኛ ንብረትም ይወድማል። ሁኔታው ያሳሰባት፣ በዚህ አካባቢ የምትገኝ አንዲት ቤተ ክርስቲያን፣ የአደጋው ሰለባ የሆኑትን ሰዎች የሚረዱ ሐኪሞችንና ነርሶችን በማሠማራት የአካባቢውን ማኅበረሰብ በንቃት ማገልገሉን ሥራዬ ብላ ተያያዘችው። የሕዝብና የመኪና ቊጥር ዕለት በዕለት እየጨመረ በመሄዱ ምክንያት ግን፣ ችግሩ በዛው መጠን ተባብሶ ቀጠለ። ይህች ቤተ ክርስቲያን እርዳታዋን በመጠንና በዐይነት ማሳደግ ብቻ ሳይሆን፣ አንድ መለስተኛ ሆስፒታል አደጋው በሚከሠትበት አካባቢ አቋቋመች። ይህ ሠናይ ምግባር የሰለባዎቹን ጤንነትና ሕይወት ከመታደግ አንጻር ብዙ ጠቀሜታ ቢኖረውም፣ ችግሩን ግን ከምንጩ ማድረቅ አልቻለም። ምክንያቱም የችግሩ ምንጭ የተሳሳተ የመንገድ ቅያስ ነውና። በመስኩ የሠለጠኑ መሐንዲሶች መንገዱን በአዲስ መልክ ቢሠሩ ችግሩ ሊፈታ እንደሚችል የትራፊክ ፖሊስ ጽሕፈት ቤቱን በቃልም ሆነ በጽሑፍ ቢያሳስቡም፣ ባልታወቀ ምክንያት ጽሕፈት ቤቱ ጆሮ ዳባ ልበስ አለ።
በየዘመናቱ ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስ ሰጠኝ የምትለውን ዐደራ ከዳር ለማድረስ፣ በሚያስፈልገው ሁሉ በመውተርተር ላይ ትገኛለች። ቤተ ክርስቲያን ነዳያንን በማብላት፣ የታመሙትን በማስታመም፣ ለመበለቶች ዳኛ በመሆን ጥልቅ ስም አላት። በርግጥም ቤተ ክርስቲያን የምስካየ ሕዙናን መንበር ናት። ወደ ፊትም ይህንኑ ግብረ ሠናይ ምግባሯን አጠናክራ መቀጠል እንዳለባት አያጠያይቅም። ነገር ግን ችግሩን በዘላቂነት መፍታት የምትችለው የተሳሳተ ፖሊሲ ያስከተለውን ፍሬ በመልቀም ብቻ ሳይሆን፣ መንግሥት ትክክለኛ ፖሊሲ እንዲነድፍ ስታሳስብ፣ መንግሥት ሲሳሳትም ስሕተቱን ስሕተት ነው ማለት ድፍረትና ክህሎት ሲኖራት ብቻ ነው።
ፖለቲካ፣ የሕዝብ አስተዳደር መዘውር ነው። ቤተ ክርስቲያን የመዘውሩ ነገር ምን ተዳዬ የምትል ከሆነ ግን፣ በመዘውሩ እክል ምክንያት በሚከሠቱ ችግሮች ላይ ብቻ መጠመዷ አይቀሬ ነው። ይህ አስተሳሰብ በክርስቲያኑ ማኅበረሰብ ውስጥ ሠርጾ በመዝለቁ ምክንያት፣ ወደ ፖለቲካው ዓለም የሚገቡ ወይም የፖለቲካ ሳይንስ የሚያጠኑ የቤተ ክርስቲያን ልጆች፣ ከመንፈሳዊነት እንደ ጐደሉ ምናልባትም ክርስቶስን ከመከተል እንዳፈገፈጉ ይታሰባል። ክርስቲያን “የዓለም ብርሃን” ነው፣ “የዓለም ጨው” ነው የሚለው የቃለ እግዚአብሔር ትምህርት፣ በፖለቲካ ሕይወት ውስጥ ጨለማና አልጫ ነው ያለው ማነው? እንዲያውም ክርስቲያኖች በንቃት ሊሳተፉበት የሚገባ፣ ጨውነታቸውንና ብርሃንነታቸውን ሊገልጡበት የሚገባው የሕይወት ክፍል ፖለቲካ ነው። እንደ ንጉሥ ዳዊት፣ እንደ ንጉሥ ሰሎሞን ያሉ የእምነት አበው ፖለቲከኞች ነበሩ። እንደ ነቢዩ ናታን፣ ነቢዩ ኢሳይያስ፣ ነቢዩ ዳንኤል፣ ነቢዩ አሞጽ ወዘተ ያሉ ነቢያት ደግሞ መንግሥትን በማማከር አገልግለው እንዳለፉ ገድላቸው ይናገራል። መንግሥት ሲስት ይገሥጹና ከስሕተቱ እንዲመለስ መንገድ ያመላክቱ እንደ

